Tuesday, September 11, 2012

የዘመን አቆጣጠር

መስከረም 1 ቀን 2004 ዓ.ም.
ባሕረ ሐሳብ ሶፍትዌርን ከዋናው ገጽ ዳውንሎድ አድርገው መጠቀም ይችላሉ
1. ባሕረ ሐሳብ ማለት ምን ማለት ነው?

ባሕረ ሐሳብ ማለት ቁጥር ያለው ዘመን ማለት ነው፡፡ በሌላ አገላለጽም የሐሳብ ባሕር ማለት ነው፡፡ በዓላት እና አጽዋማትን ለማውጣት የመደመር፣ የመቀነስ፣ የማባዛት ስሌትን ብቻ ሳይሆን ሐሳበ ፀሐይን፣ ሐሳበ ወርኅን፣ ሐሳበ ከዋክብትን ሐሳበ ዐበቅቴን ወዘተ አጠቃሎ የያዘ እንደ ባሕር የሰፋ በመሆኑ የሐሳብ ባሕር ተብሏል፡፡ የዘመን አቈጣጠር ማለት ስለማሕበራዊ ኑሮ ጠቄሜታና የሃይማኖት ተግባሮች ለማከናወን በሚያገለግል መልኩ ተፈጥሮአዊውን የወቅቶች ክፍፍል እርስ በርሳቸው የማመቻቸት ዘዴ ነው፡፡
ሐሳበ ዘመን የዘመን አቆጣጠር ማለት ሲሆን የሐሳበ ዘመን ትምህርት ባሕረ ሐሳብ ይባላል፡፡ ባሕረ ሐሳብ የሚለው ቃል ሐሰበ ቆጠረ ከሚለው ግስ የወጣ ዘመድ ዘር ነው፡፡ ስለዚህ ባሕረ ሐሳብ ማለት ቁጥር ያለው ዘመን ወይም ዓመተ ዓለም ማለት ነው፡፡ ባሕረ ሐሳብ መባሉም የባሕር አዝዋሪቱ፣ መንገዱን፣ ጥልቀቱና ስፋቱ ረዥምና ሰፊ እንደሆነ የባሕረ ሐሳብ ትምህርትም መንገዱን ስፋቱ ልዩ ልዩ በሆነ የአጽዋማትና የሱባዔያት ምሥጢር የተሰናዳ ስለሆነ ነው፡፡
በኢትዮጵያ ዘመን አቆጣጠር /የጊዜ ቀመር/ አንድ ዓመት በውስጡ ዐሥራ ሦስት ወራትን የያዘ ሆኖ በአራት ወቅቶች የተከፈለ ነው፡፡ አራቱ ክፍላተ ዘመን የሚባሉት፡- “ክረምት ከሰኔ 26 ቀን - መስከረም 25 ቀን፣ መፀው /መከር/ ከመስከረም 26 ቀን - ታኅሣሥ 25 ቀን፣ በጋ /ሐጋይ/ ከታኅሣሥ 26 ቀን - መጋቢት 25 ቀን፣ ጸደይ /በልግ/ ከመጋቢት 25 ቀን - ሰኔ 25 ቀን ናቸው፡፡ ከክረምት በስተቀር እያንዳንዱ ወቅት በውስጡ ዘጠና ዘጠና ቀናት ይዟል፡፡ ክረምት ግን ለብቻው 95 ቀናትን የያዘ ነው፡፡

2. አራቱ ክፍላተ ዘመን
የቅዱስ ያሬድ ድርሰቶች ጊዜ፣ ወር፣ ዘመን አላቸው፡፡ አንድን ዓመት በአራት ክፍለ ዘመን በመክፈል ድርሰቱን ውሱን አድርጎታል፡፡ ዘመኑም እንዲሁ በድርሰቱ የተወሰነ ሆኗል፡፡ እነዚህም ዘመናት ዘመነ መፀው፣ ዘመነ ሐጋይ፣ ዘመነ ጸደይ፣ ዘመነ ክረምት በመባል ይታወቃሉ፡፡
2.1. ዘመነ መፀው
መፀው በሌላ አነጋገር ጥቢ ይባላል፡፡ እንደ ሌሊት ከብዶ የሚታየው ክረምት አልፎ መስከረም ከጠባ በኋላ በ4ኛው ሳምንት ስለሚጀምር ነው ጥቢ የሚባል ተጨማሪ ስያሜ የተሰጠው፡፡
ዘመነ መፀው ከመስከረም 26 እስከ ታኅሣሥ 25 ድረስ ያለው ጊዜ ነው፡፡ የዕለቱ ቁጥርም 90 ይሆናል፡፡ ከዘመነ ክረምት ቀጥሎ በመሆኑ ዘመነ ክረምትን በማስቀደም ፅጌንና መፀውን በማስተባበር ቅዱስ ያሬድ የሚከተለውን ብሏል፡፡ “ግሩም በሆነው ኃይልህ እንመካ ዘንድ አንተ ዘመናትን ሠራህ ክረምትን ለዝናባት መፀውን ለአበቦች ሰጠህ” ድጓ ዘጽጌ ኩፋሌ 2 ኢዮ.2÷23 ኤር.5፥24/
መፀው መሬት በክረምት የተሰጣትን ዘር አበርክታ፣ አብዝታ ለፍሬ የምታደርስበት የምርት ወቅት ነው፤ መፀው በአብዛኛው የአዝመራ መሰብሰቢያ ጊዜው ነው፡፡ በዚህ ክፍለ ዘመን በዋናነት ሦስት ወራት ያገኛሉ፤ እነርሱም ጥቅምት፣ ኅዳርና ታኅሣሥ ናቸው፡፡ ይህ ወቅት በኢትዮጵያ ምድር አበቦች በየሜዳው በየሸንተረሩና በየተራራው ፈክተው የሚታዩበት አዝርእት የሚያሸቱበትና ለፍሬ የሚበቁበትን ወራት ይዞ ይገኛል፡፡
2.2. ዘመነ ሐጋይ /በጋ/
ዘመነ ሐጋይ ይህ የበጋ ወቅት ነው፡፡ “ሐጋይ”…. በጋ ሆነ ከሚለው የግዕዝ ቃል የተገኘ ነው፡፡ ይህም ከታኅሣሥ 26 እስከ መጋቢት 25 ቀን ያለውን ጊዜ ያጠቃልላል፡፡ ሐጋይ በጋ የጥርን፣ የየካቲትንና የመጋቢትን ወር ይይዛል፡፡
ዘመነ ሐጋይ የቃሉ ትርጓሜ ዘመነ ፀሐይ ማለት ሲሆን ሥርወ ቃሉም ኃገየ … ከሚለው ግዕዝ የተገኘ ነው፡፡ ከአራቱ ክፍላተ ዘመን አንዱ እጅ ወይም አንድ አራተኛው ሐጋይ ይባላል፡፡ የሐጋይ ፍቺ በጋ እንደሆነ ሁሉ እንዲሁም መፀውም ጸደይም በእርሱ ስም በጋ ይባላሉ፡፡ “ዘጠኝ ወር በጋ” እንዲሉ፣ አንዳንድ ጊዜም መጽሐፍት በሁለት ከፍለው ይናገራሉ፡፡ “ክረምትና በጋን አንተ ሠራህ” ፤ “በበጋም በክረምትም እንዲህ ይሆናል” /መዝ.75፥17፣ ዘካ.14፥10፣ ዘፍ.10፥22/ እንዲል ኃጋይ ማለት መገኛ መክረሚያ በጋ፣ ፀደይ፣ ደረቅ ወቅት ነው፡፡
በዚህ ወቅት በመፀው ያሸተውና ያፈራው መኸር የሚታጨድበት፣ የሚሰበሰብበትና በየማሳው ከተከመረ በኋላ የሚበራይበት፣ በጎተራ የሚከተትበት በመሆኑ “የካቲት” የሚለውን ወር ይዞ እናገኘዋለን፡፡ የግብርናው ኅብረተሰብ እህሉን በጎተራው ከትቶ ለተወሰነ ጊዜ የሚያርፍበት በመሆኑ የዓመት በዓላት እንደ ልደት፣ ጥምቀት ያሉት፣ ዘመነ መርዓዊ የሚባለው የጋብቻ ዘመን በዚህ ወቅት የተካተቱ ናቸው፡፡
2.3. ዘመነ ጸደይ /በልግ/
ዘመነ ጸደይ ማለት የቃሉ ትርጉም ዘመን በልግ ማለት ነው፡፡ ጸደይ በበጋና በክረምት መካከል የሚገኝ በውስጡ የሚያዝያን፣ የግንቦትንና የሰኔ ወራትን የያዘ ክፍለ ዘመን ነው፡፡ በመሆኑም ጸደይ የሌሎች ወቅቶችን ባሕርያት አሳምሮ የያዘ ነው፡፡ ምክንያቱም በአንድ በኩል የበልግ አዝመራ የሚታጨድበት የሚወቃበትና የሚዘራበት ሲሆን በሌላ በኩል ደግሞ ለክረምት የሚዘራ ማሳ የሚታረስበት /ለዘር ዝግጁ የሚሆንበትን ጊዜ ነው፡፡ በአብዛኛው ግን ዘመነ በልግ ነው፡፡
ቅዱስ ያሬድ በድጓው “ይሁብ ዝናመ ተወን” የበልግ ዝናምን ይሰጣል እንዳለው የበልግ ወቅት ነው፡፡ ይህም ወቅት በልግ አብቃይ በሆነው የሀገራችን ክፍል የበልግ አዝመራ የሚዘራበት፣ በልግ አብቃይ ባልሆነው ክፍል ደግሞ መሬት ለክረምቱ የዙር ጊዜ የሚያዘጋጅበት ነው፡፡ “አንድ ሰኔ የነቀለውን ሁለት ሰኔ አይተካውም” እንደሚባለው የግብርናው ኅብረተሰብ ቀጣይ የግብርና ሥራውን በትጋት የሚሠራበት ወቅት ነው፡፡
2.4. ዘመነ ክረምት
ዘመነ ክረምት ማለት ዘመነ ውሃ ማለት ነውና በዚህ ዘመን ውኃ ይሰለጥናል፡፡ ውሃ አፈርን ያጥባል፣ እሳትን ያጠፋል፣ ቢሆንም በብሩህነቱ ከእሳት፣ በቀዝቃዛነቱ ከነፋስ፣ በእርጥብነቱ ከመሬት ጋር ተስማምቶ ይኖራል፡፡
ክረምት በውስጡ አራት ወራትን /ሐምሌ፣ ነሐሴ፣ ጳጉሜንና መስከረም/ የያዘ ነው፡፡ ቅዱስ ያሬድ “ያረሁ ክረምተ በበዓመት፣ ይሰምዑ ቃሎ ደመናት፣ በየዓመቱ ክረምትን ያገባል፤ ደመናትም ቃሉን ይሰሙታል” ሲል በድጓው እንደነገረን የዘመናት ጌታ ልዑል እግዚአብሔር በየዓመቱ አዙሮ የሚያመጣልን ወቅት ነው፡፡ ደመናትም ለቃሉ ትእዛዝ ተገዢዎች በመሆን ዝናመ ምሕረቱን ጠለ በረከቱን የሚያወርዱበት ጊዜ ነው፡፡ ከሰኔ 26 እስከ መስከረም 25 ድረስ ያለውን ጊዜ ይይዛል፡፡
3. ዓመተ ወንጌላውያን
የሦስቱ ወንጌላውያን ማለትም የዮሐንስ፣ የማቴዎስና፣ የማርቆስ ዘመናት እያንዳንዳቸው ከመስከረም 1 ጀምሮ እስከ ጳጉሜን 5 ድረስ 365 ቀን ከስድስት ሰዓት ነው፡፡ ዘመነ ሉቃስ ግን ከመስከረም 1 እስከ ጳጉሜን 6 ቀን በመሆኑ 366 ቀናት ይኖሩታል፡፡
4. ወራት
በግዕዝ ቋንቋ “ወርሃ” የምንለው ቃል በአማርኛ ወር እንለዋለን ይህም ወደ ብዙ ቁጥር ሲለወጥ ወራት ይሆናል፡፡ በኢትዮጵያ ዘመን አቈጣጠር እያንዳንዳቸው 30 ቀናት ያሏቸው 12 ወራት፣ 5 ወይም በየአራት ዓመት 6 ቀናት የሆነች ጳጉሜን ያሉ ሲሆን በአውሮፓውያን አቈጣጠር ግን የየወሩ የቀናት ቁጥር ለየት ይላል፡፡

የወራቱ ስም
የግዕዝ መገኛው
አማርኛው ትርጉም
1መስከረምከረመከረመ/ረ ይጠብቃል/
2ጥቅምትጠቀመጠቀመ/ቀ ይጠብቃል/
3ህዳርኀደረአደረ
4ታኅሣሥኀሠሠፈለገ
5ጥርጠየረመጠቀ/ወደ ላይ ተመረመረ
6የካቲትከተተሰበሰበ
7መጋቢትመገበመገበ/ገ ይጠብቃል/
8ሚያዝያመሐዘተጐዳን
9ግንቦትገነባገነባ
10ሰኔሠነየአማረ
11ሐምሌሐምለለመለመ
12ነሐሴነሐሰሠራ
5.ሳምንት
ሳምንት “ሰመነ” ስምንት አደረገ ከሚለው ከግዕዝ ቃል የተገኘ ነው፡፡ በሕገ ዑደት መሠረት ዕለት ከተነሣበት ማለትም ከእሑድ እስከ እሑድ ያለው ጊዜ ሳምንት ተብሎ ይጠራል፡፡ በዚህ ሳምንት ውስጥ ያሉት ቀናት እያንዳንዳቸው 24 ሰዓት ያላቸው ናቸው፡፡ እሑድ ማለት “አሐደ” አንድ አደረገ ከሚለው የግዕዝ ግስ የተገኘ ስለሆነ ትርጉሙ አንድ ማለት ነው፡፡ ሰኞ ሁለተኛ ፣ ማክሰኞ /ማግስት/ ሦስተኛ፣ ረቡዕ አራተኛ፣ ሐሙስ አምስተኛ፣ ዓርብ ስድስተኛ ፣ቅዳሜ ሰባተኛ ቀን ነው፡፡
እግዚአብሔር አምላክ ዓለምን በስድስት ቀናት /ከእሑድ - ዐርብ/ ፈጥሮ ያረፈባትና ሰዎችም እንዲያርፉበት ያዘዛት ሰባተኛዋ ቀን በግዕዝ ቀዳሚት ሰንበት ተብላ ትጠራለች፡፡
6. የዕለታት ስያሜ
1. እሑድ ፡ አሐደ ከሚለው ግስ የተገኘ ሲሆን ትርጉሙም አንድ አደረገ /የመጀመሪያ ሆነ/ ማለት ነው፡፡ በዚህ ቀን ፍጥረታት መፈጠር ስለጀመሩ እሑድ ተብሏል፡፡
2. ሠኑይ /ሰኞ/፡ ሠነየ ከሚል ግስ የተገኘ ሲሆን ትርጉሙም ሁለት አደረገ ማለት ነው፡፡ ለሥነ ፍጥረት ሁለተኛ ስለሆነ ሰኑይ/ ሰኞ/ ተብሏል፡፡
3. ሠሉስ/ማክሰኞ/ ፡ ሠለሰ ከሚል ግስ የተገኘ ሲሆን ሦስት አደረገ ማለት ነው፡፡ ማክሰኞ የሚለው የሰኞ ማግስት ማለት ነው፡፡
4. ረቡዕ ፡ረብዐ /አራት አደረገ/ ከሚል ግስ የተገኘ ሲሆን ለሥነ ፍጥረት አራተኛ ቀን ማለት ነው፡፡
5. ሐሙስ፡ ሐመሰ /አምስት አደረገ/ ከሚል ግስ የተገኘ ሲሆን ለሥነ ፍጥረት አምስተኛ ቀን ማለት ነው፡፡
6. ዓርብ ፡ ዓረበ ከሚል ግስ የተገኘ ሲሆን ተካተተ ማለት ነው፡፡ ፍጥረታት እሑድ መፈጠር ጀምረው አርብ ስለተካተቱ /ተፈጥረው ስለተፈፀሙ/ አርብ ተብሏል፡፡
7. ቅዳሜ፡ ቀዳሚት ማለት ሲሆን ሰንበተ ክርስቲያን ከሆነችው ከዕለተ እሑድ ቀድማ ስለምተገኝ ቀዳሚት ሰንበት /ቅዳሜ/ ተብላለች፡፡
7. የ2004 ዓ.ም. የአጽዋማትና የበአላት ማውጫ
መንበር ……………………………………… 17
ወንጌላዊ ……………………………….…… ዮሐንስ
ዕለት……………………………………….... ሰኞ
ዓበቅቴ ……………………………………..... 7
መጥቅዕ …………………………………....... 23
ጾመ ነነዌ ………………………………… ጥር 28
ዓብይ ጾም………………………………… የካቲት 12
ደብረ ዘይት ……………………………… መጋቢት 30
ሆሣዕና …………………………………… መጋቢት 9
ስቅለት …………………………………… ሚያዝያ 5
ትንሣኤ …………………………………… ሚያዝያ 7
ርክበ ካህናት ……………………………… ግንቦት 1
ዕርገት ……………………………………… ግንቦት 16
ጰራቅሊጦስ ………………………………… ግንቦት 26
ጾመ ሐዋርያት …………………………… ግንቦት 27
ጾመ ድኅነት ……………………………… ግንቦት 29
ማጠቃለያ
አሁን ያለውን የዘመን አቆጣጠር አስልተን እንድንቆጥር ያደረገው የባሕረ ሐሳብ ደራሲ የሆነው የእስክንድርያ 12ኛ ጳጳስ የነበረው ቅዱስ ድሜጥሮስ ነው፡፡ ይሄ አባት በደረሰልን የቁጥር ቀመር መሠረት በዓላትን አጽዋማትን መቼ እንደሚውሉ እያሰላን እንጠቀማለን አሁንም የአቡሻህር መምህራን ከመቁጠርያቸው ጀምሮ እስከ አቆጣጠራቸው እያስተማሩ ይገኛሉ፡፡ መነሻውም መጽሐፍ ቅዱስን መሠረት አድርገው ስሌቱን እያስፋፉት ይገኛል፡፡
ምንጭ http://www.eotcmk.org/site/

6 comments:

  1. ቃለህይወት ያሰamaleን እጅግ ሚስጥራዊ ትምህርት ነው
    ገብረመድህን

    ReplyDelete
  2. እግዚአብሔር ይስጥልኝ።

    ReplyDelete
  3. please clearly tell me about the picture

    ReplyDelete
  4. http://tseday.wordpress.com/2008/09/14/ethiopian-calendar/

    ReplyDelete
  5. እግዚአብሔር ሊቃዉንተ ቤተ ክርስትያንን ይጠብቅልን ዘንድ የዘወትር ፀሎታችን ነዉ::

    ReplyDelete
  6. http://tseday.wordpress.com/2008/09/14/ethiopian-calendar/

    ReplyDelete

Thank you for your comments, we will response on timely manner.
thank you again.