Wednesday, October 3, 2012

የኢትዮጵያ ዘመን አቆጣጠር ከየት ይጀምራል?


የኢትዮጵያ ዘመን አቆጣጠር የሚጀምረው ከፍጥረተ ዓለም፣ ከፍጥረተ ጸሐይ፣ ከፍጥረተ ጨረቃ ጋር የተያያዘ ሲሆን የሚጀምረውም ጥንት ከሚለው ነው። ጥንትነቱም ከእነዚሁ ከዓለም፣ ከጸሀይ ፣ ከጨረቃና ከዋክብት መፈጠር ጋር የተያያዘ ሲሆን በጸሐይ ሶስት  ጥንታት አሉ። እነሱም፦-

1.      ጥንተ ዕለት፦ ጥንተ ዕለት እሑድ ሲሆን በዚህ ቀን ዓለም ማለትም ሰማይና ምድር የተፈጠረበት ቀን ነው።

2.     ጥንተ ቀመር፦ ይህ ዕለት ሠሉስ /ማክሰኞ/ ሲሆን በዚህ ቀን በዓለም ውስጥ የሚገኙ ፍጥረታት /ዕፅዋት፣ አዝርዕት፣ አታክልት/ ለመጀመሪያ ጊዜ የተፈጠሩበት ቀን ነው።

3.     ጥንተ ዮን፦ ጥንተ ዮን ዕለተ ረቡዕ ሲሆን በዚህም የቀንና የሌሊት መክፈያ የሆኑት ጸሐይ፣ ጨረቃና ከዋክብት የተፈጠሩበት ቀን ነው። ዮን ማለት ጸሐይ ማለት ነው። “ዮን ይዕቲ ስማ ለጸሐይ ሀገረ ጸሐይ ዮን ይዕቲ” እንዲል።

እንግዲህ የኢትዮጵያ ዘመን መቆጠር የጀመረው ዓለም ከተፈጠረበት ጊዜ ጀምሮ ነው። ስለ ዘመን ቆጠራም ስንናገር “ዓለም ከተፈጠረ ዘመን ከተቆጠረ” እንላለን። ስለዚህ ዘመን ቆጠራችን ከሥነ ፍጥረት ጋር የተያያዘ ነው።

ሥነ ፍጥረት ምን ማለት ነው?

ሥነ ፍጥረት ከሁለት ቃላት የተገኘ ሲሆን ሥን ማለት ያማረ፣ የሰመረ ማለት ሲሆን ፍጥረት ደግሞ የተፈጠረ ወይም የተገኘ ማለት ነው። ሥነ ፍጥረት ያማረ፣ የሰመረ የተዋበ ፍጥረት ማለት ነው።” ወርእየ እግዚአብሔር ኩሉ ዘገብረ ከመ ሠናይ ጥቀ - እግዚአብሔር ፍጥረታቱ ሁሉ መልካም እንደሆነ አየ’’ ዘፍ፤ 1፣21 ይላል። አንድም ሥነ ፍጥረት የፍጥረት መበጀት ወይም መሰራት ማለት ነው። የበጀ ማለት ደግም መልካም ማለት ነው። አንድም የፍጥረት መስማማት ማለት ነው። የማይስማሙና ጠበኞች የሆኑ አራቱ ባሕርያት በእግዚአብሔር ኃይል ተስማምተው ስለሚኖሩ የፍጥረት መስማማት እንለዋለን። /እንዴት ተስማምተው እንደሚኖሩ በሚቀጥለው ትምህርታችን እንመለከተዋለን/

የሥነ ፍጥረት አስገኚ ማን ነው?

በዚህ ዓለም ላይ ላሉ ነገሮች ሁሉ አስገኚ አላቸው። ለምሳሌ ሸክላ ያለሰሪ፣ ልብስ ያለ ሰፊ፣ ዕፅዋት፣ አታክልትና አዝርዕት ያለ መሬት፣ ሰው ያለእናት አባት እንደማይገኙ ሁሉ በዓለም ውስጥ ያሉ ፍጥረታት ሁሉ ያለፈጣሪ ሊገኙ አይችሉም። የሰማይ መዘርጋት፣ የምድር መርጋት፣ የቀንና የሌሊት፣ የበጋና የክረምት መፈራረቅ፤ እንዲሁም ነፋሳት፣ ደመናት፣ መባርቅት፣ ብርሃናት፣ ውሆች ሁሉ አዛዥና ገዥ፣ ፈጣሪ፣ አስገኚ እንዳላቸው ያሳያሉ።

ሥነ ፍጥረት ስንል አሁን እየተፈጠረ ያለ አዲስ ነገር አይደለም። ይልቁንም ከጥንት ጀምሮ በአባቶች ሲነገር የነበረ ነው። በአንዳንድ ሳይንቲስቶች አመለካከት በአሁን ሰዓት ሰው እያገኛቸው ያሉ ግኝቶችን ልክ አሁን እንደተገኙ ከዚህ ቀደም እንዳልነበሩ ተደርጎ ይነገራሉ። ነገር ግን ሁሉም ከጥንት ጀምሮ በአባቶቻችን በቃል ሲነገር፣ በጽሑፍ ሲሰፍር ከትውልድ ወደ ትውልድ ሲሸጋገር የኖረ ነው። በአሁን ሰዓት የሰው ልጅ ጥቂቶቹን ተመራምሮ የደረሰባቸውን በማስተዋወቅ፣ በማስረዳት በስራ ላይ እንዲውሉ፣ ለአገልግሎት እንዲበቁ  አድርጓል። ይህ ማለት ግን ያልነበረውን አዲስ ፍጥረት ፈጥሯል ማለት አይደለም። ሥነ ፍጥረት አንድ ጊዜ በእግዚአብሔር የተፈጠረ ነው። ቅዱስ ዮሐንስ “ሁሉም በእርሱ ሆነ/ተፈጠረ/፣ ከሆነውም አንዳች ስንኳ ያለ እርሱ አልሆነም” ዮሐ፤ 1፣3 እንዳለው።

እንደውም ለፈጣሪ መኖር ዋነኛው አስረጂዎች እነዚሁ ፍጥረታት ናቸው። ቅዱስ ጳውሎስ “ዓለማት በእግዚአብሔር ቃል እንደተዘጋጁ ስለዚህ የሚታየው ነገር ከሚታየው እንዳልሆነ በእምነት እናስተውላለን።” ዕብ፤ 11፣3 ይላል። እንዲሁም የማይታየውና ጥንት የማይታወቀው አምላክ በእነዚሁ በፍጥረታት አማካኝነት እንደተገኙም “ወዘኢያስተርኢ እግዚአብሔር እምፍጥረተ ዓለም ተዐውቀ በፍጥረቱ በሀልዮ ወበአዕምሮ - የማይታየው ባሕርይ እርሱም የዘላለም ኃይሉ አምላክነቱ ከዓለም ፍጥረት ጀምሮ ከተሰሩት ታውቆ ግልጽ ሆነ።” ሮሜ፤ 1፣20 በማለት የማይታየው ፣የማይጨበጠው አምላክ መኖሩ የታወቀው በፈጠረው ፍጥረት ነው።፡ማር ይስሐቅም “ወለእመ ፈቀድከ ታእምር ዘንተ ብከ ሰማዕት ወመምህር እምአፍአ ዘይመርኀከ ኀበ አእምሮተ እግዚአብሔር - የእግዚአብሔርን መኖር /ሕልውና/ ለማወቅ ከወደድክ መምህር ምስክር ሆኖ እግዚአብሐርን ወደማወቅ የሚመራህ ሥነ ፍጥረት አለልህ” /ማር ይስሐቅ እመጽሐፈ መነኮሳት ምዕ፤ 1 አንቀጽ 2/ ይላል። በእርግጥም አባቶቻን እግዚአብሔርን ፈልገው ያገኙት በፈጠረው ፍጥረት አማካኝነት ነው። ስርወ ሃይማኖት፣ አርከ እግዚአብሔር የተባለው አብርሃም በእግረ ልቡና፣ በፍኖተ አእምሮ ተጉዞ ከአምላኩ ጋር ያገናኙት እነዚሁ ፍጥረታት ናቸው። እኛ የምንኖርበትን ትንሽ ጎጆን ብንመለከት የቤቱን ጣራ ባለበት ቦታ ለማቆም ስንት ነገር ማለትም በዙሪያው የቆመው ግድግዳ፣ እርሱም ካልበቃው ቁጥራቸው እንደ ቤቱ ስፋት በሚወሰኑ ቋሚዎች /collens/ አማካኝነት ካልሆነ የቤቱ ጣራ ሊቆም አይችልም። ነገር ገን እግዚአብሔር የፈጠረውን ሰማይ ብንመለከት ይህን ያህል ከአድምስ እስከ አድማስ ሲዘረጋ መደገፊያ ግድግዳ ወይም ቋሚዎች አላስፈለጉትም። ቅዱስ ዳዊት “ሰማያት የእርሱን ጽድቅ /መኖር/ ይናገራሉ።” እንዳለው። መዝ፤ 18፣1 ፤ መዝ፤ 96፣6

እግዚአብሔር ሥነ ፍጥረትን ለምን ፈጠረ?

ከዓለማት አስቀድሞ እግዚአብሔር በአንድነት በሶስትነት /አንድነቱ ሶስትነቱን ሳይጠቀልለው፤ ሶስትነቱ ደግሞ አንድነቱን ሳይከፋፍለው/ ሲቀደስ፣ ሲሰለስ ይኖር ነበር። ባሕርይው ባሕርይውን እያመሰገነ በክብሩ በጌትነቱ ይኖር ነበረ። ዮሐ፤ 17፣5 ፤ ቅዳሴ ግሩም፤ ነገር ግን ክብሩ በራሱ ብቻ እንደቀረ ባየ ጊዜ ፍጥረታትን ልፍጠር ብሎ አሰበ። አስቦም አልቀረ ፍጥረታትን ፈጠረ። ምንና ምን ቢሉ፦

·         ሰውና መላእክትን ስሙን ለመቀደስ፣ ክብሩን ለመልበስ፣ መንግስቱን ለመውረስ፤

·         ሰማይና ምድርን ለፍጥረታት ማደርያ፤

·         አራቱን ባሕርያት /እሳት፣ ውሃ፣ ነፋስና መሬት/ ለፍጥረት መገኛ፤

·         ሌላውን ፍጥረት ለአንክሮ /እንዲደነቅበት/፣ ለተዘክሮ/ አምላክ መኖሩን ለማሳሰብ/ ለምግበ ሥጋ፣ ለምግበ ነፍስ ፈጥሯቸዋል። “ኩሉ ዘተፈጥረ ለመፍቅደ ነባብያን ቦ እምኔሆሙ ለምህሮ ወቦ እምኔሆሙ ለተገብሮ” እንዲል። ከላይ እንደተመለከትነው ለፈጣሪ መኖር ማረጋገጫ እንዲሆኑም ጭምር ፈጥሯቸዋል።

በዓለም ውስጥ ያሉ ፍጥረታት ስንት ናቸው?

እግዚአብሔር የፈጠረው ፍጥረት እያንዳንዱ ቢቆጠር ፍጡር ተናግሮ ባልጨረሰው ነበር። ይህን ያህላል ተብሎም በሰዎች አዕምሮም ሊወሰን አይችልም። ነገር ግን በየወገኑ፣ በየወገኑ፤ ብዙውን አንድ፣ ብዙውን አንድ አድርገን  ስንቆጥር ሃያ ሁለት ናቸው። “እስከ ሰባተኛይቱ ቀን ድረስ ሃያ ሁለት ፍጥረታትን ፈጠረ።” መጽ፡ ኩፋሌ፤ 3፣9 ይላል። ሊቀ ነቢያት ሙሴ የሥነ ፍጥረቱን ቁጥር የሃያ ሁለቱ አርእስተ አበው ምሳሌ አድርጎ ተናገሯል። እነዚህ አርዕስተ አበው ከአዳም ጀምሮ እስከ ያዕቆብ ድረስ ያሉ ናቸው። “ከአዳም ጀምሮ እስከ ያዕቆብ ድረስ ያሉ አበው ሃያ ሁለት ናቸው።” ኩፋ፤ 3፣9

እንዲሁም አዳም በገነት እያለ ይጸልይባቸው የነበሩ በኋላም ቅዱስ ዳዊት በመዘሙሩ ያነሳቸው ስመ አምላክ /የአምላክ ስሞች ሃያ ሁለት ናቸው። እነዚህም “አሌፍ፣ ቤት፣ ጋሜል፣ ዳሌጥ፣ ዋው፣ ዛይ፣ ሔት፣ ጤት፣ … ታው” መዝ፤ 118፣1 ያሉት ናቸው። ስለዚህ የሃያ ሁለቱ ፍጥረታት ቁጥር ከእነዚህ ጋር የተያያዘ ነው።    

 የሃያ ሁለቱ ሥነ ፍጥረት መገኛ

ፍጥረታት የተፈጠሩት በሁለት  መንገድ ሲሆን እነሱም፦

·         እምኀበ አልቦ ኀበ ቦ - ከምንም ምን ወይም በባዶ፦ ካለምንም  የተፈጠሩ ሰባተት ፍጥረት ሲሆኑ እነሱም እሳት፣ ውሃ፣ ነፋስ፣ መሬት፣ ጨለማ፣ ሰባቱ ሰማያት እና መላዕክት ናቸው።

·         ግብር እምግብር ወይም ፍጥረት እምፍጥረት፦ እነዚህ ከአንድና ከዚያ በላይ ከሆኑ ፍጥረታት የተፈጠሩ ሲሆኑ ከላይ ከተጠቀሱት ሰባቱ ፍጥረታት ውጪ ሌላው አስራ አምስቱ በዚህ መልክ የተፈጠሩ ናቸው። መገኛቸውም ከአራቱ ባሕርያት /ከእሳት፣ ከውሃ፣ ከነፋስና ከሬት/ የተፈጠሩ ናቸው።  

ፍጥረታት ሲፈጠሩ በሶስት ዓይነት ሁኔታ ነው፦

·         በአርምሞ፦ በዝምታ ወይም ባለመናገር ሲሆን በአርምሞ የተፈጠሩ ሰባት ፍጥረታት ናቸው። እነሱም፦ አራቱ ባሕርያት፣ ጨለማ፣ ሰማያትና መላዕክት ናቸው።

·         በነቢብ /በመናገር/፦ በመናገር የተፈጠሩ አስራ አራት ፍጥረታት ሲሆኑ እነሱም ከብርሃን ጀምሮ ያሉ አስራ አራቱ ፍጥረታት ናቸው።

·         በገቢር / በመስራት /፦ በገቢር የተፈጠረው ሃያ ሁለተኛው ፍጥረት  አዳም ብቻ ሲሆን ከምድር አፈር አበጃጅቶ በሰባት ባሕርያት አጽንቶ ፈጥሮታል። ዘፍ፤ 2፣7 እነዚህ ሰባት ባሕርያት የሚባሉት አራቱ ባሕርያተ ሥጋ እሳት፣ ውሃ ፣ ነፋስና አፈር እንዲሁም ሶስቱ ባሕርያተ ነፍስ የሚባሉት ሕያውነት/ዘላለማዊነት/ ፣ ነባቢነት/ተናጋሪነት/ እና ለባዊነት/አስተዋይነት/ ናቸው።

በሚቀጥለው ከእሑድ እስከ ሰኞ የተፈጠሩትን ሃያ ሁለቱን ሥነ ፍጥረታት እንመለከታለን። ይቆየን


        

No comments:

Post a Comment

Thank you for your comments, we will response on timely manner.
thank you again.