Saturday, January 12, 2013

ወንበር

በዓላትንና አጽዋማትን ለማውጣት ከሚያስፈልጉን ነገሮች ውስጥ አንዱ መጥቅዕ ሲሆን በዓላትና አጽዋማት የሚያድሩባቸውን ሌሊት የሚያሳውቀን ደግሞ አበቅቴ ነው። አበቅቴና መጥቅዕ በየዘመኑ የሚቀያየሩ ስለሆነ ሁልጊዜ ማለትም በየዓመቱ የየዘመኑን አበቅቴና መጥቅዕ ማውጣት ይኖርብናል። እንግዲህ ወንበር እነዚህን አበቅቴንና መጥቅዕን የምናወጣበት ቁጥር ነው። ወንበር የሚለው ስያሜ የተገኘው አበቅቴም ሆነ መጥቅዕ /ለበዓላትና ለአጽዋማት መገኘት ወሳኙ የሆኑ ነገሮች/ የሚገኝበት ከመሆኑም በላይ ዓመቱን ሙሉ ቀሚ በመሆን የሚያገለግል ቁጥር ስለሆነ ነው።

ወንበር እንዴት ይወጣል?
ወንበርን በተለያየ መንገድ ማውጣት የምንችል ሲሆን ሊቃውንት አባቶቻችን እንደ ዛሬው የሂሳብ መቀመሪያ መሳሪያዎች ሳይኖሩ የሂሳብ ስሌቶችን የሚሰሩት በቃላቸው ነበር። አሁንም አብዛኛዎቹ በቃላቸው ነው የሚሰሩት። ለምሳሌ አንድን ትልቅ ቁጥር ለሆነ ቁጥር ማካፈል ቢፈልጉ /ለምሳሌ 7450ን ለ532 ለማካፈል/ የሚጠቀሙት እንደኛ ካልኩሌተር ሳይሆን በቃላቸው ነው የሚያካፍሉት። በዚህን ጊዜ ይንን ትልቅ ቁጥር ለማካፈል የተለያዩ መንገዶችነ ይጠቀማሉ። ስለዚህ ይህንን የአባቶችን ትውፊት መተው ተገቢ ስላልሆነ እንዲሁም አንዱም መንገድ በመሆኑ እንመለከተዋለን። ሌላው ደግሞ ዘመኑ የሰጠንን አጭር መንገዶችንም መጠቀሙ ለስራችን ቅልጥፍና የሚሰጠው በመሆኑ በዘመናዊ መንገድ በማለት እንመለከተዋለን።